የቻይና ፍርድ ቤቶች በ2016 ከ1 ነጥብ 4 ሚሊየን የማያንሱ ጥንዶችን የፍቺ ጉዳይ መፈፀማቸውን የሀገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ገለጸ፡፡

በተመሳሳይ ዓመት በፍርድ ቤት የፍቺ ጥያቄ ካቀረቡት ውጭ 3 ነጥብ 46 ሚሊየን ቻይናውያን ጥንዶች፥ በማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ በኩል ፍቺ መፈፀማቸውን የቻይና ህዝባዊ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከፍተኛ ባለስልጣን ዱ ዋንሁዋ ተናግረዋል፡፡

የፍርድ ቤት ዳኞች ለፍቺ በቀረቡት መዝገቦች መሰረት የቤተሰብ ችግሮችን ለማስታረቅ ማህበራዊ እና ስነልቦናዊ ጉዳዮችን እንዳጣሩ ነው ዱ የጠቀሱት፡፡

በዚህም መሰረት 10 ሚሊየን ሰዎች በቀጥታ በችግሩ ውስጥ የተሳተፉ ሲሆን፥ ልጆችን፣ ቤተሰብን እና የቅርብ ዘመዶችን ጨምሮ 50 ሚሊየን የሚሆኑ ሰዎች በፍቺው ምክንያት ለጉዳት ተጋልጠዋል፡፡

የሀገሪቱ ማህበራዊ ጉዳዮች ሚኒስቴር እንዳስታወቀው በፈረንጆች 2014 በማህበራዊ ጉዳይ ቢሮዎች በኩል 2 ነጥብ 96 ጥንዶች የተፋቱ ሲሆን በ2015 ደግሞ 3 ነጥብ 15 ሚሊየን ጥንዶች ተፋትተዋል፡፡

ምንጭ፡-https://guardian.ng