የአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ በ10 ሚሊየን ብር ወጪ የሁለት ታሪካዊ ሃውልቶች እና ቤቶች እድሳት ሊያከናውን ነው፡፡እድሳት የሚደረግላቸው የአፄ ምኒሊክና የአፄ ቴዎድሮስ ሴባስቶፓል ሃውልቶች፣ የከንቲባ ገብረፃዲቅ ጎሹ እና የሼሆ ጀሌ መኖሪያ ቤቶች ናቸው፡፡በቢሮው የቱሪዝም ልማት ቅርስ አስተዳደር ዋና የሥራ ሂደት የቱሪዝም መረጃ ኬዝ ቲም አስተባባሪ አቶ ሳሙኤል ሠይፉ ለኢዜአ እንደገለጹት፥ ሃውልቶችቹንና ታሪካዊ ቤቶቹን የማስዋብና የማልማት ተግባር በማከናዋን የከተማውን መስህብነት እንዲጨምር ያደርጋል፡፡በተለይም የቱሪስት መዳረሻ መስህቦች፣ ታሪካዊ ቦታዎች፣ አብያተ ክርስቲያናት፣ ሙዚየሞች፣ ታሪካዊ ሃውልቶችና ቤቶች ቱሪስቶች ሊመለከቷቸውና ሊጎበኟቸው ከሚፈልጉት መካከል ናቸው ብለዋል።ሐውልቶቹን ለማደስበ2008 ዓ.ም እቅድ ተይዞ እንደነበር ያስታወሱት አቶ ሳሙኤል፥ የጨረታ ጉዳይና ተያያዥ ጥናቶች ባለመጠናቀቃቸው መዘግየቱን ተናግረዋል።በዚህ ዓመት ስራውን ለማስጀመር የዝግጅት ተግባራት እየተከናወነ መሆኑንም ነው የተናገሩት።ከ7 ነጥብ 8 ሚሊየን ብር በላይ በማውጣት የቱሪስት መዳረሻና መስህብ ቦታዎች በፅሁፍ መረጃ የሚሰጥ የቱሪስት የጉዞ መመሪያ መውጣቱንም ገልጸዋል።በዋና ዋና መንገዶች ላይ 17 የቱሪስት የከተማ ካርታዎች መተከላቸውን የጠቀሱት አስተባባሪው፥ ባለፈው ዓመት የአዲስ አበባ ሙዚየም፣ የአራት ኪሎና የስድስት ኪሎ የሰማዕታት ሃውልቶች የጥገናና የእድሳት ሥራ መከናወኑን አስታውሰዋል፡፡