የአሜሪካው የካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ አዲስ ያወጣው ጥናት ነገሮችን መስጋት በርካታ ጠቀሜታዎች እና በጎ ጎኖች እንዳሉት ያመለክታል።

ተመራማሪዎች በጥናቱ ላይ የምንሰጋ ከሆነ የተከላካይነት እና ራስን የመጠበቅ ባህሪያችን እንዲነቃቃ ከማድረግ አንጻር ያለውን ሚና ለይተዋል።

በሪቨር ሳይድ ካፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ የስነ አእምሮ ፕሮፌሰር ኬይት ስዊኒ፥ ስጋት በእኛ ላይ የሚያስከትለው መጥፎ ጎኑ እንዳለ ሆኖ መልካም ጎኖች እንዳሉት ጥናቱን በማስመልከት በሰጡት መግለጫ ላይ አስታውቀዋል።

ስጋት ያለን ተነሳሽነት እንዲጨምር በማድርግ የስሜት መነቃቃትን ይፈጥራል ሲሉም ፕሮፌሰር ኬይት ተናግረዋል።

ስጋት አሊያም አብዝቶ ማሰብ ከአሰቃቂ ገጠመኞች እያገገምን መሆኑን፣ ለነገሮች እቅድና ዝግጅት እደረግን መሆኑን እንዲሁም ከድብርት እያገገምን መሆኑን ሊያመላክት እንደሚችልም ጥናቱ አስቀምጧል።

በጥናቱም ነገሮችን ይሰጋሉ ተብለው የተለዩ ሰዎች በስራ ቦታም ሆነ በትምህርት ቤት ከልሎች የተሻለ አፈጻጸም ሲያስመዘግቡ የታለየ ሲሆን፥ ችግሮችን በመቅረፍ ላይም ስኬታማ ናቸው ይላ ጥናቱ።

ስጋት እርምጃ ልንወስድባቸው እና ልናስተካክላቸው ለሚገቡ ነገሮች እንደ ማስጠንቀቂያ ምልክትነት እንደሚያገለግል የተገለፀ ሲሆን፥ ስጋት የሚስተዋልባቸው ሰዎችም ጭንቀታቸውን ለመቀነስ እርምጃ እንዲወስዱ እና እንዲወስኑ እንደሚረዳቸው በጥናቱ ተብራርቷል።

ስጋት በሽታዎችንም ቀድመ ለመከላከል ይረዳል የተባለ ሲሆን፥ ለምሳሌም ስለ ቆዳ ካንሰር አብዝተው የሚያስቡ ሰዎች ሰን ስክሪንን በመጠቀም ቀድመው ሲከላከሉ ይስተዋላል ብለዋል።

ይህ እንደማሳያነት ተነሳ እንጂ ስጋት እና በሽታን ቀድሞ የመከላከል ባህሪ የሚገልጹ በርካታ ምሳሌውች እንዳሉም ነው ፕሮፌሰር ስዊኒ ሚናገሩት።

ለነገሮች መካከለኛ በሚባል መልኩ የሚሰጉ ሴቶች ከመጠን በላይ ከሚሰጉ እና ምንም ስጋት ከሌለባቸው ሴቶች ጋር ስነጻጸሩም፤ ከመጠን በላይ የሚሰጉ እና ምንም ስጋት የሌለባቸው ሴቶች የካንሰር ተጋላጭነት ከፍ ብሎ ተገኝቷል ብለዋል።

ይህም ለነገሮች አሳሳቢ ለሆኑ ነገሮች እምብዛም አለመስጋት እና ከመጠን በላይ መስጋት ጉዳት እንዳለው ያመላክታል ያሉት ፕሮፌሰሯ፥ ለነገሮች በመጠኑ ማለትም መካከለኛ በሆነ መስጋት ግን ጠቀሜታ እንዳለው ያመላክታል ብለዋል።

በጣም ከመጠን ያለፈ ስጋት ወይም ፍራቻ በሰዎች ጤና ላይ ጉዳት እንደሚያስከትልም ነው ፕሮፌሰር ስዊኒ የሚናገሩት።

ለነገሮች በመጠኑ የሚሰጉ ሰዎች ምንም ስጋት ከሌለባቸው ጋር ሲነጻጸሩ በልክ አሊያም መካከለኛ በሆነ መጠን የሚሰጉ ሰዎች የበለጠ እና የተሻለ ጠቀሜታ የሚያገኙ መሆኑንም አብራርተዋል።

ምንጭ፦ www.upi.com/Health