ሙሉቀን  ቸርነት  ተካሳሽ ነው፡፡  ከሳሽ ደግሞ የፌደራሉ ዓቃቤ ህግ ሲሆን ግለሰቡ የተከሰሰበት የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው ተከሳሹ የፀና የንግድ ፈቃድ ሳይኖረው በንግድ ዓለም በመሰማራቱ ነው ይላል፡፡

ሲዘረዘር ተከሳሽ የሚኖረው በጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 05 ክልል ውስጥ ልዩ ቦታው ቀጨኔ ሁለገብ ተብሎ በሚጠራው ስፍራ አካባቢ በቤት ቁጥር 9999 ውስጥ ነው፡፡

በዚሁ መኖሪያ ቤቱ ውስጥ ወሩና ቀኑ ባልታወቀ ከ2007 ዓመተ ምህረት ጀምሮ ቤቱ እስከታሸገበት እለት መስከረም 23 ቀን 2009 ዓ.ም ድረስ ቤቱን ያለፈቃድ በጋራዥ ስራ መልክ ሲሰራበት በመገኘቱ ለክሱ ምክንያት መሆኑ ተጠቁማል፡፡

ጉዳዩን ሲመለከት የሰነበተው የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ አንደኛ ወንጀል ችሎት የዓቃቤ ህግን የሰነድ፣ የሰውና ሌሎች የኢግዚቢት መረጃዎችን በማየት ውሳኔ አስተላልፎበታል፡፡

ተከሳሹ ካቀረባቸው የቅጣት መቅለያዎች መካከል ገሚሶቹን በመውሰድና የአቃቤ ህግ የቅጣት ማክበጃ አለማቅረቡን ከግምት ውስጥ በማስገባትእጁ ከተያዘበት ከታህሳስ 3 ቀን 2009 ጀምሮ በሚታሰብ የአራት አመት ከስምንት ወር ጥኑ እስራትና በአምስት ሺህ ብር እንዲቀጣ ግንቦት 11 ቀን 2009 ዓ.ም ውሳኔ አስተላልፎበታል፡፡