የቴክኖሎጂ ኩባንያው ጎግል እና የልብስ አምራቹ ሌቪስ በአይነቱ ለየት ያለ ስማር ጃኬት መስራታቸውን አስታውቀዋል።የቴክኖሎጂ እና የልብስ አምራች የሆኑት ሁለቱ ግዙፍ ኩባንያዎች በጥምረት በመሆን የሰሩት ስራ የቴክኖሎጂ እና የፋሽን ዓለምን አንድ ላይ የሚያስተሳስር ነው ተብሏል።ኩባንያዎቹ በአንድ ላይ በመሆን የዓለማችንን የመጀመሪያ ስማርት ጃኬት የሰሩ ሲሆን፥ ጃኬቱ ውስጥም የኤሌክትሮኒክስ ክሮች እንዲገቡ ተደርጎ ነው የተሰራው።

“ፕሮጄክት ጃኩዋርድ” በመባል የሚጠራው የስማርት ጃኬት ስራው እንደ አውሮፓውያን አቆጣጣር በ2015 የተጀመረ ሲሆን፥ “Commuter™” በሚል የንግድ ስያሜም ተሰጥቶታል።

አዲሱን ስማርት ጃኬት ከስማርት ስልካችን ጋር በቀላሉ ማገናኘት የምንችል ሲሆን፥ ስልካችንን ከኪሳችን ውስጥ ሳናወጣ በስማርት ጃኬቱ ብቻ ስልክ ማነጋጋር፣ ሙዚቃ ማዳመጥ፣ አቅጣቻዎችን ለማወቅ እና መሰል ተግባራትን ለማከናወን ያስችለናል። ስማርት ጃኬቱ ከስልካችን ጋር የምናገናኘው በብሉቱዝ መሆኑም ተነግሯል።ሙዚቃ ለማዳመጥ አሊያም ሰዓት ለማወቅ ጃኬቱን በእጃንም መዳበስ አሊያም በሁለት ጣታችን ብቻ መንካት በቂ ነው ተብሏል።