የቴክኖሎጂ አምራቹ ኖኪያ እና የማህበራዊ ትስስር ድረ ገጹ ፌስቡክ መረጃን በፍጥነት በማስተላለፍ አዲስ ክብረወሰን መስበራቸው ተነግሯል።ኩባንያዎቹ በባህር ስር በሚዘረጋው የፋይበር ኦፕቲክስን በመጠቀም በአንድ ሰከንድ 32 ቴራ ባይት (32 ሺህ ጊጋ ባይት) መረጃን ማስተላለፍ በመቻላቸው ነው ክብረወሰኑን ሊሰብሩ የቻሉት።

ኖኪያ እና ፌስቡክ አዲስ የሞከሩት መረጃ የማስተላለፍ ፍጥነት አሁን በጥቅም ላይ ካለው ኦፕቲካል ማስተላለፊያ በ2 ነጥብ 5 እጥፍ እንደሚፈጥን ነው የተነገረው።

ሙከራውም 5 ሺህ 500 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለውና ከአሜሪካዋ ኒውዮርክ እስከ አየርላንድ በባህር ስር በተዘረጋው የፋይበር ኦፕቲክስ መስመር ላይ ነው የተካሄደው።

በፌስቡክ ኩባንያ የዓለም አቀፍ ኦፕቲካል ኔትዎርክ አርኪቴክት የሆኑት ስቴፈን ግረብ፥ “ፌስቡክ የቀጣዩ ትውልድ የፈጠራ እና ቴክኖሎጂ የማላመድ ፍጥነቱ እንዲጨምር ይፈልጋል” ብለዋል።

“ከኖኪያ ጋር የተደረገው ሙከራም የባህር ስር ኦፕቲካል ፋይበርን በመጠቀም መረጃን የማስተላላፍ ፍጥነት እና አቅም ከዚህም መጨመር እንደሚችል የሚያሳይ ነው፤ ይህም አሁንም በዘርፉ የምናደርገውን ጥረት መጨመር እንዳለብን ያሳያል” ሲሉም ተናግረዋል።እንዲሁም በቀጣይ በባህር ስር በኦፕቲካል ፋይበር አማካኝነት የሚተላለፍ የመረጃ ዋጋ በበይት እንዲቀንስ እናደርጋለን ነው ያሉት።

የኖኪያ ኦፕቲካል ኔትዎርኪንግ ሀላፊ ሳም ቡኪ፥ “ከአጋራችን ፌስቡክ ጋር በመሆን በኦፕቲካል ፋይበር አማካኝነት መረጃን በፍጥነት ለማስተላለፍ የሚሰራውን ስራ አጠናክረን አንቀጥላለን ብለዋል።

ምንጭ፦ www.techworm.net