መጪውን የትንሳኤ በዓል ምክንያት በማድረግ ከአዲስ አበባ ወደ ተለያዩ ክልሎች የሚደረገው ጉዞ የትራንስፖርት አቅርቦት ችግር እንደገጠመው የፌደራል ትራንስፖርት ባለስልጣን አስታወቀ፡፡

ከዚህ ቀደም ከ5 እስከ 6 አውቶቢሶች የሚጠይቁ መስመሮች አሁን እስከ 30 መጠየቃቸውን ባለስልጣኑ ገልጿል፡፡ባለስልጣኑ ችግሩን ለመፍታት የትራንስፖርት ማህበራቱ ከመደበኛ ውጭ በፍቃደኝነት መስመር እንዲይዙ እና በጭማሪ ክፍያ እንዲሰሩ እየተሰራ መሆኑን ገልጿል፡፡

የባለስልጣኑ የኮሚኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ይግዛው ዳኘው እንዳሉት ህብረተሰቡ በዓሉን ከቤተሰቦቹ ጋር እንዲውል ለማስቻል በኮሚቴ ችግሮችን ለመፍታት ጥረት እየተደረገ ነው፡፡በበዓሉ የሚፈጠሩ ወከባዎችን እና ስርቆትን ለመቀነስም ከፖሊስ ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን  አቶ ይግዛው ገልጸዋል፡፡

በአዝመራው ሞሴ